Tuesday, December 25, 2012

የመነኮሳት ሕይወት

የመነኮሳት ሕይወት
አባ መቃርስ መነኮስ
ሁላችሁ ቅዱሳኑ፥ እግዚአብሔርን ውደዱት፤ እግዚአብሔር እውነተኞችን ይፈልጋል፥ ትዕቢተኞችንም ፈጽሞ ይበቀላቸዋል። በእግዚአብሔር የምታምኑ ሁላችሁ፥ በርቱ ልባችሁም ይጥና። መዝ.፴፡፳፫
“ካህንሰ እምኢተምህረ እምኢያ ብዝኃ ስብሐተ ትኅርምተ እምኢመጽኦ ትምክህት” /”ካህን ብዙ በዘይማር ትዕቢት ኩራት ባልወጣበት በነኮስም ትኅርምት አበዛለሁ ባይል ትምሂት ባልመጣበት ነበር።”/ (አባ መቃርስ መነኮስ)
አባታችን አባ መቃርስ ከሰው ርቆ ንጽህናውን ጠብቆ በበረሃ ይኖር ነበር። ምግቡ ቆቅ ነበር። በየቀኑ አንድ አንድ ቆቅ እየተያዙለት ቀቅሎ ሲባርከው ጎመን እየሆነለት ይመገበው ነበር። አንድ መነኩሴ ከቁስጥንጥያ መጥቶ እሱ ካለበት በረሀ ሲገባ ሲያጠምድ አይቶ ለሐሜት ቸኩሎ ወደ ከተማ ተመልሶ ለሊቀጳጳሱ ነገረው። እርሱም ሰርክ ሲደርስ ሊያጠምድ ወጣ። ሦስት ቆቆችን አጠመደ፤ ሊፈትነኝ ነውን ወይስ ሆዴ አልጠግብ ብላ ይሆን አለ። ወዲያው እኒህ መነኮሳት ካጠገቡ ደርሰው “ሰላም ለከ ኦ አቡነ” አሉት ጌታ ባወቀ ያደረገው ነው ብሎ ደስ አለው። አብስለሎ ድርሻቸውን ሰጣቸው። እርሱም ድርሻውን በልቶ መለስ ቢል አስቀምጠው ሲያዩት አያቸው፤ ለምን እራታችሁን አልበላችሁም? አላቸው። እኛስ እንዲህ ዓይነቱን እንበላ ዘንድ አልተፈቀደልንም አሉት። እሱን ለመንቀፍ እንደሆነ አውቆ እፍ እፍ ቢላቸው በረው ሄደዋል። በከንቱ አምተነዋል፤ ብለው ከእግሩ ወድቀው ይቅርታ ጠይቀውታል።
ሲነጋ ወደ ከተማ ተመልሰው ያዩትን ለሊቀጳጳሳቱ ነገሩት። እሱም እንዲህ ያለ ጻድቅ በዘመናችን ተገኝቷልና እጅ ነስተን እንምጣ ብለው ከንጉሱ ላከበት። ንጉሥ ሠራዊቱ፣  ሊቀጳጳሳቱ፣ ካህናቱን አስከትለው ከበዓቱ ሲደርሱ የታዘዘ መልአክ መቃርስን ወደ ብሔረ ሕያዋን ሲያደርሱ አዩ። “ባርከነ ኦ ቅዱሱ ለእግዚአብሔር ወንግረነ አሐተ ቃለ”  አባታችን ባርከን አንዲት ቃልም ንገረን አሉት። “ካህንሰ እምኢተምህረ እምኢያ ብዝኃ ስብሐተ ትኅርምተ እምኢመጽኦ ትምክህት” ካህን ብዙ በዘይማር ትዕቢት ኩራት ባልወጣበት በነኮስም ትኅርምት አበዛለሁ ባይል ትምሂት ባልመጣበት ነበር። ብሎ ተናግሯቸውና ባርኳቸው ዐርጓል። የአባታችን ፍልሰቱ  በታኅሳስ ፲፫ ነ። የአባታችን በረከት፣ ጸጋ፣ ምልጃ፣ ቃልኪዳን በሁላችን ላይ ጸንቶ ይኑር አሜን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

/
ምንጭ፦ መዝገበ ታሪክ ዘኦርቶዶክስ ተዋህዶ

No comments:

Post a Comment