Tuesday, August 7, 2012

አባ ሕርያቆስ በትምህርቱ መናፍቃንን ተከራክሮ ይመልሳልና ብለው ግብረ ገብም ከሆነ ይሾም ብለዋል:በጸሎቱ ይጠብቃል..


ሕርያቆስ ማለት ህሩይ ማለት ነው : ለሹመት መርጠውታልና: አንድም ረቂቅ ማለት ነው ምሥጢረ ሥላሴን ይናገራልና : ከሊቃውንትስ ምሥጢረ ሥላሴን የማይናገር የለም ብሎ ከሁሉ ይልቅ እሱ አምልቶ አስፍቶ አጉልቶ ይናገራልና አንድም ፀሐይ ማለት ነው: አብ ፀሐይ ወልድ ፀሐይ መንፈስቅዱስ ፀሐይ ብሎ ጽፏልና : አንድም ብርሃን ማለት ነው: የምዕመናንን ልቦና በትምህርቱ ብሩህ ያደርጋልና : ዘአብርሃ መንበረ ማርቆስ በብርሃን እንዲል :አንድም ንብ ማለት ነው: ንብ የማይቀምሰው አበባ የለም እሱም የማይጠቅሰው ሊቅ የለም:ይህም እንደምን ነው ቢሉ:ሐዋርያት የተማረ ግብረ ገብ ይሾም ብለው ሥራት ሰርተዋል: ይህስ አይደለም ሁለቱን አስተባብሮ የያዘ አይገኝም ብሎ የተማረ ከሆነ ይሾም ብለዋል::በትምህርቱ መናፍቃንን ተከራክሮ ይመልሳልና
ብለው ግብረ ገብም ከሆነ ይሾም ብለዋል:በጸሎቱ ይጠብቃል: በትሩፋቱ ያጸድቃል:ትምህርቱን ውሎ አድሮ ያደርገዋልና ብለው ሾሙት :ይህም አባ ሕርያቆስ ያልተማረ ግብረ ገብ ነው :ቢማርም ለጸሎት ለቅዳሴ ያህል ነበር:በብህንሳ 10000 መነኮሳት 10000 መነኮሳይያት ተሹሟል በብዙም መሾም ልማድ ነው::

አባ ሆርና አባ ኤስድሮስ 1000 አባ አሞን 3000 አባ ጳኩሚስ 6000 አባ ሰራብዮን 10000 ተሾሙ:ይህችም ብህንሳ ቅድመ ትሰይም አርጋድያ ወድህረ መኑፍ ይላል: ብዙ ግዜ ስመ ተፋልሶ አግኝቷታል :በፊት አርጋድያ ኋላም መኑፍ ተብላለች ዛሬም ብህንሳ ትባላለች:ሴትና ወንድ ያልተለየባት ገዳም ናት:እንደ ዘጌ እንደ ቆራጣ እንደ ቀንጠፋሜ እርሱም ግብረ ገብ ነውና ሥራት ቢያጸናባቸው ይጣሉታል:ያልተማረ ነውና ይንቁታል: ከመጠምጠም መማር ይቅደም እንዲሉ ከመሾም መማር አይቀድምምን እያሉ; እሱ ግን ወእቀውም ዮም በትህትና ወበፍቅር ብሎ እንዲያመጣው: እንደጠሉኝ ልጥላቸው እንደ ናቁኝ ልናቃቸው ሳይል በፍቅር እና በትህትና ጸንቶ ያስተምራቸው ነበር::


ከዕለታት ባንዳቸው በምን ምክንያት እንሻረው አሉ:ቀድሰህ አቁርበን ብለን በዚህ ምክንያት እንሻረው ብለው መክረው ቀድሰህ አቁርበን አሉት: የሱ ግን ተምኔቱ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም የእመቤቴ ምስጋና እንደባህር አሸዋ እንደ ሰማይ ኮከብ በዝቶልኝ እንደምግብ ተመግበው እንደ መጠጥ ጠጥቼው እንደ ልብስ ለብሼው እያለ ይመኝ ነበር:ቅዳሴ ገብቶ ሥርዓቱን ጨርሶ ከፍሬ ቅዳሴው ሲደርስ ከሊቃውንት ቅዳሴ የሚያስቸግር የማንን እናውጣለት እያሉ ሲያወጡ ሲያወርዱ የለመኗትን የማትነሳ የነገሯትን የማትረሳ እመቤት ገልጻለት ጐሥዓ ልብየ ቃለ ሠናየ ብሎ ወይእዜኒ ንሰብሐ እስኪል ድረስ ሰተት አድርጎ ተናግሮታል: የሚንቁት የሚጠሉት ይህ የነገሩትን ቀለም እንኳን አከናውኖ መናገር የማይችል ዛሬስ እንግዳ ድርሰት እደርሳለው ብሎ አገኝ አጣውን የቆጥ የባጡን ይቀባጥራል: ብለው አደነቁበት የሚወዱት የሚያከብሩት ከመንፈስቅዱስ ነው እንጂ እንዲ ያለ ምሥጢር ከእሩቅ ብዕሲ ይገኛልን ብለው አደነቁለት: ወዲያው የሚወዱት የሚያከብሩት ጽፈን ደጉሰን አንይዘውምን አሉ: የሚንቁት የሚጠሉት ደግሞ ማን ተናገረው ብለን እንይዘዋለን አሉ እንደ ልማዱ አድርገን አንይዘውም አሉ:: ለሃገራቸው እንግዳ ድርሰት የተደረሰ እንደሆነ ጽፈው ደጉሰው ከእሳት ይጥሉታል: ከእሳት ደህና የወጣ እንደሆነ ከውሃ ይጥሉታል ከውሃ የወጣ እንደሆነ ከህሙም ላይ ይጥሉታል ድውይ የፈወሰ እንደሆነ ደገኛ ድርሰት ነው ብለው ይይዙታል::

ይህንንም ቅዳሴ ማርያም ጽፈው ደጉሰው ከእሳት ላይ ጣሉት ከእሳት ደህና ወጣ: ከውሃ ጣሉት ከውሃ ደህና ወጣ: ከህሙም ላይ ጣሉት ድውይ ፈወሰ: ይልቁንም ሙት አስነስቷል:: ደገኛ ድርሰት ነው ብለው ጽፈው ደጉሰው ይዘውታል:በጥራዝም 14 አድርገው ጠርዘውታል: 14 ቅዳሴም ተአምራት ያልተደረገበት የለም: የቀደሰበት ምን ቀን ነው ቢሉ: ከእመቤታችን 33 በዓላት ባንዱ ቀን ነው: አንድ ባህታዊ ከባለሟልነት የተነሳ 33 በዓላት ማንን ትወጃለሽ ብሎ እመቤታችንን ጠየቃት:ኪዳነምህረትን ልደታን አስተርአዮን ፍልሰታን አለችው: ከሊህ 4ቱስ ማንን ትወጃለሽ ቢላት ከጸባብ ወደ ሰፊ: ከጨለማ ወደ ብርሃን: የወጣውበት ነውና ልደቴን እወዳለው አለችው: ቀድሞ እነ ሳልወለድ እናትና አባቴን መባችሁን አንቀበልም ብለው አዝነው ተክዘው ነበር: የነሱ ሃዘን ሃዘኔ ነውና እኔን ከወለዱ በኋላ መባቸውን ተቀብለዋቸው ደስ ብሎዋቸዋል: የነሱ ደስታ ደስታዬ ነውና እንዳለችው የልደታ እለት ነው የቀደሰው:: እሱስ ማንን ሊቀድስ ኖሯል ቢሉ ከቅዳሴ ሐዋርያት ሌላ አያቅም ነበርና ቅዳሴ ሐዋርያትን: ይህስ አይደለም ለእመቤታችን ቅዳሴ ሐዋርያት ምኗ ነው: ምን ቢቸግር ተበድሮ ጋሬዳ እንዲሉ ቅዳሴ እግዚእን ሊቀድስ ነበር ስሟን ባያነሳ እምድንግል ተወሊዶ ከመ ፈቃድከ ይፈጽም ብሎ በምሥጢር ያነሳታል::


ከባህር ወዲህስ ማን አምጥቶልናል ቢሉ ቅዱስ ያሬድ ማይ ኪራህ መደባይ ታብር በሚባል ቦታ ይኖር ነበር እመቤታችን ቅዱስ ኤፍሬምን ከሶርያ አባ ሕርያቆስን ከብህንሳ በደመና ጠቅሳ ያሬድ ካለበት አድርሳ አንተ ውዳሴዬን አንተ ቅዳሴዬን ነግራችሁት በዜማ ያድርስ ብላቸው እነሱም ነግረውት በዜማ አድርሶታል:: ከዚሁ አያይዞ 13ቱንም ቅዳሴ በዜማ ደርሷል: ይህም ሊታወቅ ሥረይ በቅዳሴ ማርያም ይበዛል::ከተከዜስ ወዲህ ማን አምጥቶልናል ቢሉ ሳሙኤል ትውልደ ጌዴዎን ዘገበዘ አክሱም ይለዋል እሱ አምጥቶልናል እሱም ይሄን እየደገመ ሲሄድ ክንድ ከስንዝር ከመሬት መጥቆ ይሄድ ነበር: ከዕለታትም በአንዳቸው ውሃውን ቢባርከው ህብስት ሆኖለት ተመግቦ ምዕመናንን መግቧቸዋል:: እመቤታችንም የፍቅር ምልክት ሁለት ንዋያት ሰታዋለች ነጭ እጣን እና እንቁ ነው: ከዛም አያይዛ ውዳሴዬን ከቅዳሴዬ ጋራ አንድ አድርጎ የሚደግመውን ሰው አንተ ከገባህበት ውሳጤ መንጦላዕት አገባዋለው:ብላ ተስፋውን ነግራዋለች:: ይህውም ሊታወቅ ዛሬ በዋልድባ ያጠና በቃሉ: ያላጠና በመጽሃፍ ቅዳሴ ማርያም ሳይደግም የሚውል የለም:ይህም ተስፋ ውዳሴዋን ከቅዳሴዋ ጋር አንድ አድርጎ ለምደግም ሰው ሁሉ ነው:እንጂ ለሱ ብቻ አይደለም:አንድ ባህታዊ ከምስጋናሽ ሁሉ ማንን ትወጃለሽ ብሎ ቢጠይቃት ልጄ ዳዊትን አቡነ ዘበሰማያትን ቢደግሙለት እንዲወድ እኔም ውዳሴዬን ቅዳሴዬን ቢደግሙልኝ ወዳለሁ ብላዋለች ::
አባ ሕርያቆስ ተሹሞ ሳለ ብዙ ድርሳንን ደርሷል ብዙ ተግሳጽ ጽፏል ከብዙውም አንዱ ይህ ቅዳሴ ማርያም ነው እረፍቱ በጥቅምት 2 ነው::
 አኮቴተ ቁርባን ዘእግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ ዘደርሰ በመንፈስቅዱስ አባ ሕርያቆስ ኤጲስ ቆጶስ ዘሃገረ ብህንሳ ጸሎታ ወበረከታ የሃሉ ምስለ ኩሎሙ ህዝበ ክርስቲያን ለዓለመ ዓለም አሜን፡፡
ኃጥያታችንን ከሚያስተሰርይልን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አሜን !!!!!: ምንጭ ፡- ቅዳሴ ማርያም አንድምታ

2 comments:

  1. ኃጥያታችንን ከሚያስተሰርይልን ልጅሽ ጽንዕት በድንግልና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን አሜን !!!!

    ReplyDelete