Tuesday, July 24, 2012

መላእክትን ‹‹ያድናሉ›› ማለት ስሕተት ነውን?


ለመሆኑ መላእክት ማዳን ይችላሉ ማለት ስሕተት ነውን? ዛሬ ዛሬ ብዙዎች መናፍቃን መላእክትን ‹‹ያድናሉ›› ማለት እንደ ስሕተትና እንደ ክህደት ቆጥረውት ሲናገሩ መስማት የተለመደ ሆኗል፡፡ ለምን ሲባሉም መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹መዳን በሌላ በማንም የለም›› በማለት ያለ አገባቡ ጥቅስ ይጠቅሳሉ፡፡

በእርግጥ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹መዳን በሌላ በማንም የለም›› ይላል፡፡ ይሁን እንጂ ይህ መላእክት አያድኑም ማለት አይደለም፡፡  
ቅዱስ ዳዊት በግልጥ ‹‹የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፤ ያድናቸውማል›› ይላል፡፡ (መዝ33.7) ጥቅሱ ‹‹ያድናቸውማል›› ማለቱን ልብ በሉ፡፡ መላእክት የማያድኑ ቢሆኑ ኖሮ ቅዱስ ዳዊት በዚህ መልኩ ግልጥ አድርጎ ‹‹ያድናቸውማል›› ይል ነበር? መጽሐፍ ቅዱስ ከመሰከረው እውነት የሚበልጥ ዕውቀት አለንን? እርሱ ‹‹ያድናሉ›› እያለ እኛ ‹‹አያድኑም›› ብንል ምን ማለታችን ነው? ይህ ጥቅስ ውሸት ነውን? ይህንን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል እንታዘዘዋለን? እናምነዋለን? ወይስ ልናርመው እንወዳለን?

በሌላም የመጽሐፍ ቅዱስ ገጸ ንባብ ውስጥ ‹‹ከክፉ ነገር ሁሉ ያዳነኝ መልአክ እርሱ እነዚህን ልጆች ይባርክ›› በማለት ያዕቆብ የልጅ ልጆቹን እንደባረከ እናነባለን፡፡ (ዘፍ48.16) በዚህ ጥቅስ ውስጥ መልአክ ‹‹ከክፉ ነገር ሁሉ›› እንደሚያድን በግልጽ ተጽፏል፡፡ መላእክት ‹‹ያድናሉ›› ላለማለት እነዚህን ግልጽ ቃላት መላእክት ይጠብቃሉ፤ ይራዳሉ፤ ያግዛሉ በማለት ማድበስበስ ይኖርብን ይሆን? ይህ ሁሉ ዝርዝሩ ሥራቸው ቢሆንም እንደሚድኑም ተጽፏልና ማመን ያስፈልጋል፡፡

በዚህ መልኩ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ የተናገረውን ቃል እናቶችና አባቶች በስእለታቸው ‹‹ቅዱስ ሚካኤል አድነኝ፤ ቅዱስ ግብርኤል ድረስልኝ›› እያሉ በመድገማቸው የዋሃን ስለሆኑ መጽሐፍ ቅዱስ ስለማያውቁ ነው መባል አለባቸው? ቅዱስ ዳዊትና ቅዱስ ያዕቆብ የመላእክትን አዳኝነት በግልጽ ያወጁት መጽሐፍ ቅዱስን ወደ መንፈሳዊ ኮሌጅ ገብተው ስላልተማሩ ይሆን? ወይስ አንድ ሰባኪ የመላእክትን አዳኝነት ስላስተማረ ‹‹ገድል ጠቃሽ›› በሚል መጥላላት አለበት? ዘማርያኑስ በዚህ መልኩ መዘመራቸው ሊያስወቅሳቸው ይገባ ነበር?


መላእክት የእግዚአብሔር ናቸው፡፡ የፈጠራቸው እርሱ ነው፡፡ የሚፈጽሙትም የእርሱን ፈቃድ ነው፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ የእርሱ መሆናቸውን በሚያሳይ አገላለጥ ‹‹መልአኩ፣ የጌታ መልአክ፣ መላእክቱ›› እያለ ይጠራቸዋል፡፡ ‹‹የጌታ መልአክ በሕልም ታየው›› እንዲል፡፡ (ማቴ1.20) መላእክት ሲያድኑ ፈጣሪ ሥራ አልሠራም ማለት አይደለም፡፡ መላእክት ያለ እርሱ ፈቃድ ምንም ሊያደርጉ አይችሉም፡፡ ሥራ እንዲሠሩ የሚፈቅድላቸውና የሚያዛቸው እርሱ ነው፡፡ ስለዚህ እነርሱ የሠሩትን ይዘን ‹‹ፈጣሪ ይህን አደረገ ማለት እንችላለን›› እርሱ አዟቸውና ፈቅዶላቸው እስከሠሩት ድረስ እርሱ ሠራ ማለት ነውና፡፡ የሚቀጥሉት ሦስት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምሳሌዎች ይህን ሐሳብ የሚያስረዱ ናቸው፡፡

ለምሳሌ፡- ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ጅራፍ እንዲሠሩ አዘዛቸው፡፡ ራሱ ግን ጅራፍ አልሠራም፡፡ ቢሆንም ግን መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ እንደሠራ አድርጎ ‹‹የገመድ ጅራፍ አበጅቶ›› ይላል፡፡ (ዮሐ2.15) ዳግመኛም ኢየሱስ ክርስቶስ ማንንም አላጠመቀም ሐዋርያቱ ግን እንዲያጠምቁ አዟቸዋል፡፡ ያዘዛቸው እርሱ በመሆኑ ‹‹ያጠምቃል እጅግም ደቀመዛሙርት ያደርጋል›› የሚል ወሬ በፈሪሳውያን ዘንድ ተሰምቷል፡፡ ራሱ ግን ማንንም አላጠመቀም ነበር፡፡ (ዮሐ4.1-3) ሌላ ምሳሌ ለመጨመር እነ ሐና እና ቀያፋ ራሳቸው ኢየሱስ ክርስቶስን አልሰቀሉትም፡፡ ነገር ግን ተባባሪዎችና ትእዛዝ ሰጪዎች ስለነበሩ ቅዱስ ጴጥሮሰ ‹‹እናንተ በሰቀላችሁት›› ሲል ሰቃዮች መሆናቸውን ጠቅሶ ወቅሷቸዋል፡፡ (የሐዋ4.10)

በአንጻሩ ደግሞ ሥልጣኑ የፈጣሪ ነው ማለት መላእክት ‹‹ይህን ሠሩ›› አይባልም ማለት አይደለም፡፡ ፈጣሪ በመላእክት ሲሠራ መላእክትን እንደ ቁስ ቆጥሮ ይሠራባቸዋል ማለት አይደለም፡፡ መላእክት ሕያዋን ናቸው፡፡ የማዘንና የመደሰት ስሜት አላቸው፡፡ ባይሆን ኖሮ ንስሐ በሚገባ ኃጢአተኛ ደስ እንደሚላቸው አይጻፍም ነበር፡፡ ስለዚህ መላእክት ደስ እንደሚሰኙ ሁሉ ያዝናሉ ማለት ነው፡፡ ፈጣሪ ሲያዛቸው በፈቃደኝነት ይታዘዛሉ፡፡ ፈጣሪ በእነርሱ ይሠራል ማለት ያለፈቃዳቸው ይልካቸዋል ማለት አይደለም፡፡ እንደ ሰው ልጅ ነጻነት አላቸው፡፡ ቢሆንም በእርሱ ፈቃድ ደስ ስለሚላቸው ከፈቃዱ ፈቀቅ አይሉም፡፡ ነጻ ፈቃድ ባይኖራቸው ኖሮ ሰይጣን በደለኛ ሆኖ አይገኝም ነበር፡፡ የሰይጣን ወደ ገዛ ፈቃዱ ማዘንበል ለመላእክት የተሰጣቸውን ነጻነት ያሳያል፡፡ ታዲያ ሥራቸውን ወደው የሚሠሩ ሆነው ሳለ ፈጣሪ ልኮአቸው መላእክት ቢያድኑ ‹‹አላዳኑም›› እንዴት እንላለን? ለማዳን ፈቃደኛ ሆነው እስካዳኑ ድረስ ‹‹አድነዋል፣ ያድናሉ›› ማለት የሚገባ አይደለምን?

መላእክት እግዚአብሔር ስለፈቀደላቸው የሠሩትን ሥራ እነርሱ አልሠሩትም ካልን ሰይጣን የፈጸመውን የጥፋት ተግባር ማን ሠራው ልንል ነው? መቼም እግዚአብሔር ሳይፈቅድለት ሰይጣንም ቢሆን ያሰበውን ማከናወን እንደማይችል የታወቀ ነው፡፡ ታዲያ ሰይጣን የሠራውን ፈቃጁ አካል እግዚአብሔር ስለሆነ ፈጣሪ ይህን አደረገ እንጂ ሰይጣን ይህን አልሠራውም እንላለንን? እንዲሁም ፈቃጁና አዛዡ ምንም ፈጣሪ ቢሆን ቅዱሳን መላእክት የሠሩትን እንደሠሩት ማመንና መመስከር ይገባል፡፡ ለክፉ ሥራው ሰይጣን ኃላፊነቱን እንደሚወስድ ሁሉ ቅዱሳን መላእክትም ለሥራቸው ኃላፊነቱን ይወስዳሉ፡፡ ስለዚህ ፈጣሪ ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ ቂርቆስንና ኢየሉጣን ስላዳነ ‹‹ቅዱስ ገበርኤል አዳናቸው!›› የሚገባ ነው፡፡

በቅዱሳን መላእክት ማዳንና ተራዳኢነት ውስጥ የእግዚአብሔር ሥልጣንና አዛዥነት በረቂቅ አለበት፡፡ እግዚአብሔር ሰዎችን ለማዳን በምንም መንገድ ቢሠራ በዛ ውስጥ የእርሱ ሥልጣንና ሥራ የማይጠረጠር ነው፡፡ መላእክት ያለ ፈጣሪ ትእዛዝና ፈቃድ አንዳች ሊሠሩ አይችሉም፡፡ ፈጣሪ ግን ያለ መላእክት አጋዥነት የፈለገውን የሚሠራ ሁሉን ቻይ አምላክ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ፈጣሪ ይህን ሠራ ስንል መላእክትን ላይጨምር ይችላል፡፡ መላእክት ይህን አደረጉ ስንል ግን በምንም ተአምር ከፈጣሪ ውጭ ሊሆን አይችልም፡፡ ስለዚህ መናፍቃን ‹‹ጌታ፣ እግዚአብሔር ይህን አደረገ›› ብቻ እንድንል የሚፈልጉት ቅዱሳንን ላለማስገባት ነው፡፡ እኛ ኦርቶዶክሳዊያን ቅዱሳን መላእክትንና ቅዱሳን ሰዎችን ይህን አደረጉ የምንለው እግዚአብሔርን ከማመን ጋር ስለ ቅዱሳን ክብር ለመመስከር ነው፡፡

እሳት በባሕርይው የሚፋጅ መሆኑ ይታወቃል፡፡ እንጨትና ብረት ግን ብቻቸውን ሳሉ ቢነኳቸው አያቃጥሉም፡፡ ነገር ግን ከእሳት ጋር ከተዋሐዱ /ከጋሉ/ በኋላ ቢነኳቸው ይፋጃሉ፡፡  እሳት የተዋሐደው ብረት የማያቃጥልበት ምንም ሁኔታ የለም፡፡ ካላቃጠለ ወይ እሳት አልተዋሐደውም ወይም ደግሞ እሳቱ ራሱ አያቃጥልም ማለት ነው፡፡ እንደዚሁም እግዚአብሔር በባሕርይው አዳኝ ነው፡፡ መላእክት አያድኑም ካልን ወይ እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር አይደለም ማለት ነው ወይም ደግሞ እግዚአብሔር ራሱ አያድንም እንደማለት ይቆጠርብናል፡፡ ስለዚህ ‹‹መላእክት ያድናሉ›› ስንል የሚያድን እግዚአብሔር ከእነርሱ እንደማይለይ እየመሰከርን መሆኑን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡
 የእግዚአብሔር ቸርነት
የመልአኩ የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አይለየን!
 ዲያቆን ኅብረት የሺጥላ

9 comments:

  1. በቅዱሳን መላእክት ማዳንና ተራዳኢነት ውስጥ የእግዚአብሔር ሥልጣንና አዛዥነት በረቂቅ አለበት፡፡

    ReplyDelete
  2. kale Hiwot Yasemalin Des yemil new

    ReplyDelete
    Replies
    1. ቃለህይወትን ያሰማልን ገነት መንግስተ ሰማያትን ያዋርስልን፡ የጠፉትን እና በጥርጥር ያሉትን ሁሉ የልድያን ልብ የከፈተ ጌታ አይነ ልቦናቸውን ያብራልን አሜን፡፡

      Delete
  3. ቅዱስ ገብርኤል ራሱ ‹‹እኔ በእግዚአብሔር ፊት የምቆመው መልአኩ ገብርኤል ነኝ፡፡›› በማለት ተናግሯል፡፡ ይህም በቅዱስ ወንጌል የተጻፈ ኃይለ ቃል ሲሆን አብዛኞቻንን እናውቀዋለን፡፡ ልዩ የሚሆነው ግን የቃሉን ትክክለኛ አገባባዊ ትርጉም ባለማወቃችን ምክንያት መልአኩ ይህን ባለ ጊዜ ‹‹እኔ አማላጅ ነኝ›› እንዳለን አድርገን አለመረዳታችን ነው፡፡ መቆም ማለት ማማለድ የሚል ትርጉም ካለው ‹‹በእግዚአብሔር ፊት የምቆም›› ማለት ደግሞ ‹‹የማማልድ›› ማለት መሆኑ አይጠረጠርም፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ገብርኤል አማላጅነቱን ራሱ ግልጽ በሆነ መንገድ ነግሮናል ማለት ነው፡፡

    ReplyDelete
  4. Ezih ga meleyet yalebin neger yale yimeslegnal.Ye Kirstos Eyesus Adagninet ye NEFIS dihinetin sihon yih dihnet ye Melaekt siltan alemehonun lib linil yigebal. Melaekit be Sigawi hiwotachin ke mekera ena ke teleyayu fetenawoch liyadinun yichlalu betechemarim sile nifis dihnetachin ke Egziabhere liyamalidun ena lileminulin yichilalu. Liyunetu yih yimeslegnal.

    ReplyDelete
  5. ቃለህይወትን ያሰማልን ገነት መንግስተ ሰማያትን ያዋርስልን፡ የጠፉትን እና በጥርጥር ያሉትን ሁሉ የልድያን ልብ የከፈተ ጌታ አይነ ልቦናቸውን ያብራልን አሜን፡፡

    ReplyDelete
  6. ቃለህይወትን ያሰማልን ገነት መንግስተ ሰማያትን ያዋርስልን፡ የጠፉትን እና በጥርጥር ያሉትን ሁሉ የልድያን ልብ የከፈተ ጌታ አይነ ልቦናቸውን ያብራልን አሜን፡፡

    ReplyDelete
  7. ቃለ ህይወትን ያሰማልን መንግስተ ሰማያትን ያውርስልን!!!!!

    ReplyDelete
  8. ሚስተር ቤንጃሚን የኢሜል ዝርዝሮችን እነሆ ፣ Lfdsloans@outlook.com ፡፡ / ወይም ደግሞ ንግዴን ለመጀመር በ 90,000.00 ዩሮ ብድር የረዳኝ WhatsApp + 1-989-394-3740 እና እኔ በጣም አመስጋኝ ነኝ ፣ እዚህ አንድ ነጠላ እናት ነገሮች እንዳላደረጉ መንገድ ለመፍጠር እየሞከርኩ ነው ፡፡ ከእኔ ጋር ቀላል ይሁኑ ግን ንግዴ እየጠነከረ ሲመጣ እና እያሰፋ ሲሄድ እያየሁ በሚስተር ሚስተር እርዳታ ፊቴ ላይ ፈገግታ አሳየኝ ፡፡ የገንዘብ ድጋፍን መፈለግ ወይም በዚያ ንግድ ውስጥ መከራን ማለፍ ወይም የመነሻ የንግድ ሥራ ፕሮጀክት መጀመር መፈለግ ይህንን ማየት እና ከችግራቸው ለመውጣት ተስፋ ሊኖረው ይችላል ... እናመሰግናለን ፡፡

    ReplyDelete