Thursday, February 9, 2012

ካህናት እና ዲያቆናትእንደታሰሩ ነው

(በወንድማችን ነቢዩ ሰሎሞን)
የስልጢ ቅበት ማርያም አገልገይ ካህናት ዲያቆናት እና አስተዳዳሪ አሁንም እንደታሰሩ ነው ሙሉ ሪፖርቱ ደርሶናል
በክርስቲያኖች ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ ከሚደረግባቸውና እንደ አንድ ዜጋ እንኳን ከማይቆጠሩበት ቦታዎች መካከል ስልጢ ዋናውና ቀዳሚው እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በእርግጥ በስልጢ ወረዳ ውስጥ 22 አብያተክርስቲያናት እና ከፍተና ቁጥር ያለው ምዕመን ቢኖርም እስከአሁን ድረስ ምዕመናን በነጻነት የእግዚአብሔርን ስም እንዳይጠሩ እና በነጻነት እንዳይንቀሳቀሱ ለኑሮዋቸውም ምንም ዓይነት ዋስትና የሌላቸው መሆኑ በጣም የሚያሳዝን እየሆነ መጥቷል፡፡
ይህ በምዕመናን እና በቤተክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ ያለው ከፍተኛ ተጽእኖ እና ጥላቻ እየ
በረታ ሄዶ ህዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም የቅድስት አርሴማ ቤተክርስቲያን በፖሊስ እና በከተማው ነዋሪዎች መፍረሱ ይታወሳል፡፡ በዚህ አልበቃ ያለው በክርስቲያኖች ላይ እየተደረገ ያለው ግፍ ከዕለት ወደ ዕለት በመንግስት አካላት ምንም ዓይነት መፍትሔ ሊሰጠው ባለመቻሉ አሁንም በማን አለብኝነት የወረዳው ፖሊስ እና ህዝብ ከፍተኛ ግፍና በደል እያደረሱ ይገኛሉ፡፡
ጥር 30 ቀን ያለምንም ምክንያት እና የተከሰሱበት ሁኔታ ምን እንደሆነ ሳያውቁ
1. መልአከ ስብሐት አፈወርቅ ከበደ የቅበት ቅድስት ማርያም ቤ/ክ አስተዳዳሪ
2. ቀሲስ ሲሳይ ተስፋዬ
3. ዲ/ን ሰሎሞን አሰፋ
4. ዲ/ን ቴዎድሮስ በለው
5. ዲ/ን አምታታው ግርማ
6. መ/ር ጥላሁን እንዳለ
7. አቶ ተስፋዬ ገ/ጻድቅ
8. አቶ መለሰ አሰፋ
9. አቶ አሸናፊ ግዛው
10. አቶ ነጋሽ አሰፋ
በፖሊስ ተይዘው የታሰሩ ሲሆን እስካሁን ድረስ የዋስ መብታቸው እንዳልተከበረላቸው እና ቤተሰብም እንዳይጠይቃቸው እንደተደረገ ሊጠይቁ ለመጡ የቤተሰብ አካላትም ከፍተኛ ማስፈራሪያና ዛቻ እየተደረገባቸው እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከእማኝ መረጃዎች እንዳገኘነው ፖሊስ ካህናቱን እና ምእመናንን የያዘበት ምክንያት አሳማኝ እና በቂ እንዳልሆነ እና ካስፈለገም የዋስ መብት ሊሰጣቸው እንደሚገባ የሚያስረዳ ሲሆን ለሽፋን ህል የታሰሩበት ምክንያት
1. ስለተቃጠለችው ቤተክርስቲያን ለማስረዳት ወደክልሉ መንግስት ማለትም አዋሳ ሄደው ሲመለሱ የከተማውን ሕዝብ በጥብጠዋል
2. ፖሊስ ቤተክርስቲያኒቱን ያለምንም የፍርድ ቤት ትዕዛዝ በማን አለብኝነት ሊያፈርስ ሲል እንቅፋት ሆናችኋል
3. ፖሊስ የቤተክርስቲያኑን ጉልላት እና ጣሪያ ባፈረሰ ማግስት የፖሊስ ጣቢያን በመውረር አጥር ለማፍረስ ጥረት አድርጋችኋል የሚሉ እና ሌሎች ልክ እንደዚህ ያሉ በሬ ወለደ ዓይነት ውሸት የተሞላባቸው የክስ ዝርዝሮች መሆናቸውን መረዳት ችለናል፡፡
ከዚህ በተያያዘ ፖሊስ ጉልላቱን ካፈረሰ በኋላ ቤተክርስቲያኑን ለማቃጠል ሲያስተባብሩ ከነበሩት መካከል ከድር ጀማል እና ሌሎች ሰባት ወጣቶችን ለይስሙላ ካህናቱን ባሰረበት ዕለት አስሮ የነበረ ቢሆንም ከጠዋቱ ጀምሮ በከተማው ከፍተኛ ሰልፍ በመደረጉ እና ይህ ሰልፍ እስከሚፈቱ ድረስ የሚቀጥል እንደሆነ በማሳወቃቸው ቀድሞውንም ለይስሙላ አስሯቸው የነበሩትን አስተባባሪዎች ከሰኣት ላይ ያለ ምንም ጥያቄና የፍርድ ቤት ትእዛዝ(ማለትም በዕለቱ) በ2000 ብር ዋስ እንዲፈቱ ተደርጓል፡፡ በጣም አስገራሚ የሆነው እና ለሁላችንም ግልጽ ያልሆነው ጉዳይ ዋነኛው እና በክርስቲያኖች ላይ በግልጽ ጅሃድ ያወጀው እና ከፍተኛ ቅስቀሳ እያደረገ የሚገኘው ጀማል ሽኩሪ የተባለ ሰው እስከ አሁን ድረስ ምንም ዓይነት የህግ እርምጃ ያልተወሰደበት መሆኑ ነው፡፡
ዛሬ ባደረግነው ማጣራት ያለ ህግ አግባብ የታሰሩት ካህናት እና ምእመናን ነገ የካቲት 2 ቀን 2004 ዓ.ም ፍርድ ቤት እንደሚቀርቡ ለማወቅ ችለናል፡፡
እግዚአብሔር ለነዚህ ጠንካራ አገልጋዮች እና ምዕመናን ብርታትን እና ጥንካሬን እንዲሰጥ ሁላችንም ልንጸልይ ይገባል፡፡


2 comments: